54 ሚሊዮን ብር የሚገመቱ የማቀዝቀዣ እና የመኖ ማጓጓዣ ተሽከርካሪዎች ለኅብረት ሥራ ማኅበራት ድጋፍ ተደረገ።
ባህርዳር መስከረም 15 ፣ 2017 ( እ/ዓ/ሃ/ል/ጽ/ቤት)የአማራ ክልል እንስሳት እና ዓሣ ሃብት ልማት ጽሕፈት ቤት ከክልሉ እንስሳት እና ዓሳ ዘርፍ ልማት ፕሮጀክት በተገኘ የበጀት ድጋፍ በእንስሳት ሃብት ልማት ላይ ለተሰማሩ የወተት ኅብረት ሥራ ማኅበራት እና ዩኒየኖች ድጋፍ አድርጓል።
የአማራ ክልል እንስሳት እና ዓሳ ሃብት ልማት ጽሕፈት ቤት ምክትል ኀላፊ ነጋ ይስማው እንዳሉት ፕሮጀክቱ ላለፉት ስድስት ዓመታት የክልሉን እንስሳት ሃብት ልማት ለማሳደግ የተለያዩ ድጋፎችን አድርጓል። አሁን ላይም በፕሮጀክቱ የተደረገው ድጋፍ የክልሉን የእንስሳት ሃብት ምርት ለማሻሻል አቅም እንደሚፈጥር ገልጸዋል። ማኅበራት ያገኙትን ድጋፍ ለታለመላቸው ዓላማ በማዋል ከራስ አልፈው ለሀገር የሚተርፍ ሥራ እንዲሠሩም አሳስበዋል።
የአማራ ክልል እንስሳት እና ዓሣ ዘርፍ ልማት ፕሮጀክት አሥተባባሪ ሙሉቀን ዘሪሁን
ፕሮጀክቱ ባለፉት ስድስት ዓመታት በ15 ወረዳዎች 36 ሺህ ተጠቃሚዎችን የያዘ 2 ሺህ 700 የጋራ ፍላጎት ያላቸውን ቡድኖች ማደራጀት ተችሏል። እነዚህን ቡድኖች በሂደት ወደ 128 ኅብረት ሥራ ማኅበር እና 14 ዩኒየኖች ማሳደግ መቻሉን ገልጸዋል።
የተደራጁ ማኅበራትን አሠራራቸውን በማሻሻል ተጠቃሚነታቸውን እንዲያሳድጉ ፕሮጀክቱ የአቅም ግንባታ ሥልጠና ከመስጠት ባለፈ በመኖ፣ በእንስሳት ጤና፣ የእንስሳት ዝርያ ማሻሻል ላይ ትኩረት አድርጎ ሢሠራ ቆይቷል ብለዋል።
የወተት ማቀነባበሪያ ሼዶችን በመገንባት፣ ማቀነባበሪያ ማሽኖችን፣ ተሽከርካሪዎችን እና ሌሎች አሥፈላጊ ግብዓቶችንም ድጋፍ ማድረጉንም ገልጸዋል። በዛሬው ዕለትም ግምታቸው 54 ሚሊዮን ብር የሚገመቱ 4 ማቀዝቀዣ የተገጠመላቸው መኪኖች፣ 2 የተቀነባበረ መኖ ማጓጓዣ መኪኖች፣ 10 የወተት ማጓጓዣ ባለ ሦስት እግር ካርጎ ባጃጆች ለ16 የወተት ኅብረት ሥራ ማኅበራት ርክክብ መደረጉንም ተናግረዋል።
ፕሮጀክቱ ባለፉት ስድስት ዓመታት የእንስሳትን ምርታማነትን ለማሳደግ 1 ነጥብ 1 ቢሊዮን ብር ሥራ ላይ ማዋሉን ገልጸዋል።
የሳንቃ ገነት ወተት ልማት ኅብረት ሥራ ማኅበር ተወካይ ኀላፊ መኳንንት ሞላ እንዳሉት በተሽከርካሪ ችግር ምክንያት በወቅቱ የተመረተውን ወተት ለደንበኞች ለማድረስ ይቸገሩ ነበር። በዚህም የምርት ብክነትም ያጋጥማቸው እንደነበር ገልጸዋል። አሁን ላይ ማቀዝቀዣ የተገጠመለት ተሽከርካሪ ድጋፍ መደረጉ ችግሩን እንደሚያቃልለው ገልጸዋል። ፕሮጀክቱ ባለፉት ዓመታት በሥልጠና እና በቁሳቁስ ድጋፍ ማድረጉን አንስተዋል።
የወደራ ሁለገብ ኅበረት ሥራ ማበራት ዩኒየን ሥራ አስኪያጅ አስገልለው ሙሉሸዋ ዩኒየኑ የእንስሳት መኖ ማቀነባበር ሥራ እያከናወነ ቢገኝም በተሽከርካሪ ምክንያት በወቅቱ ለደንበኞች ለማድረስ ችግር ኾኖባቸው ቆይቷል። የተበረከተላቸው የጭነት ተሽከርካሪ ችግሩን ያቃልላል ብለዋል። ፕሮጀክቱ ላደረገላቸው ድጋፍም አመሥግነዋል።