ዜና
የተሻሻለ የቤተሰብ ደሮ እርባታ የሙከራ ትግበራ የሚተገበርባቸዉ ሞዴል መንደሮች በተመለከተ የግንዛቤ መፍጠሪያ መድረክ ተካሄደ
የፌደራል ግብርና ሚኒስቴር በአገር አቀፍ ደረጃ የተሻሻለ የቤተሰብ ደሮ እርባታ የሙከራ ትግበራ ለሚካሄድባቸዉ ወረዳዎች እና የተመረጡ ሞዴል መንደሮች በተመለከተ የሚመለከታቸዉ አጋር አካላት በተገኙነበት ግንቦት 25/2013 በባህርዳር ከተማ የግንዛቤ መፍጠሪያ መድረክ አካሄደ፡፡
በመድረኩ በግብርና ሚኒስቴር የደሮ እርባታ ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር ሆኑት ወ/ሮ ጽጌረዳ ፍሬዉ የሙከራ ፕሮጀክቱን አስመልክቶ መነሻ የመወያያ ጽሁፍ አቅርበዋል፡፡
በቀረበዉ ጽሁፍ ፕሮጀክቱ እንደ ሀገር በ27 ወረዳዎች በአማራ ክልል ደግሞ በ7 ወረዳዎችና 35 ሞዴል መንደሮች ፣ በአንድ ሞዴል መንደር 60 ተሳታፊዎች( ተጠቃሚዎች) ያሉት ሆኖ በእያንዳንዱ ወረዳ 1 መኖ ማቀነባበሪያ እና 2 የ 1 ቀን የኮይኮይ ደሮ ዝርያ ጫጩት አሳዳጊዎች ተደራጅተዉ ወደ ስራ የሚገቡ መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡ ሀላፊዋ አክለዉም ለዚህ ፓይለት ፕሮጀክት ማስፈጸሚ የሚሆን እንደ ሀገር 187 ሚሊዮን ብር የተመደበ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ ከዚህ ዉስጥ ከፍተኛዉ በጀት ለመሰረተ ልማት እና ለግብአት አቅርቦት ሚዉል መሆኑን ገልጸዉ ቀሪዉ ብር ለተደራጁ ወጣቶችና ሴቶች በብድር መልክ ቀርቦ ለደሮ እና ለመኖ ግዥ አገልግሎት ሚዉል መሆኑን አሳዉቀዋል፡፡
በመድረኩ የተገኙ ተሳታፊዎችም በቀረበዉ የመወያያ ጽሁፍ ላይ ሰፊ ዉይይት ካደረጉ በኋላ ፕሮጀክቱ በቀጣይ 3 አመታት ለሚተገብራቸዉ ስራዎች ስኬታማነት የበኩላቸዉን ሀላፊነት እንደሚወጡ ገልጸዋል፡፡ የምክክር መድረኩም በዚሁ ተጠናቋል፡፡